የሥልጠና ዝርዝር

3.1 መደበኛ ገለጻ- አካል ጉዳት በሕግ ውስጥ

  • ለመድልዎ መፈጸም ጭብጦች የሆኑ ምሳሌዎችን እንዲለዩ ተሳታፊዎችን በመጠየቅ ይህን ክፍል ይጀምሩ፡፡ መድልዎን የሚከለክል ሕግ በአሁኑ ጊዜ ለሥራ ስምሪት መድልዎ መልስ እንደ መሠረታዊ ነገር እየታየ መሆኑን ለተሳታፊዎች በአጽንኦት ያሳስቡ፡፡ የመድልዎ አልባ ሕግ ዓላማ በአካል ጉዳት፣ እንዲሁም በሌሎች ጭብጦች፣ ላይ ተመሥርቶ የሚፈጸም መድልዎን ለመከልከል ነው፡፡
  • የገለጻ ማሳያ 39ን በመጠቀም በክፍለ ትምህርት 2 ውይይት የተደረገባቸው አንደ መድልዎ አልባነት፣ የዕድል እኩልነት፣ እኩል አያያዝና አዎንታዊ እርምጃዎች ያሉ አንዳንድ የመድልዎ አልባነት ሕግ ጽንሰ ሃሳቦች፣ እንዲሁም በዚህ ክፍለ ትምህርት ዘግይቶ ውይይት የሚደረግባቸውን ተመጣጣኝ ማመቻቸትና ያልተመጣጠነ ሸክምን በአጭሩ ያብራሩ፡፡

    መድልዎ አልባነት፡- በሥራ ስምሪትና በሙያ የሚፈጸም መድልዎን በሚመለከት የወጣው የዓሥድ ድንጋጌ ቁጥር 111 መድልዎን በሥራ ስምሪት ወይም በሙያ አያያዝ የዕድል እኩልነትን የመጉዳት ወይም ዋጋ የማሳጣት ዓላማ ወይም ውጤት ያለው  በዘር፣ በቀለም፣ በፆታ፣ በሃይማኖት፣ በፖለቲካዊ አመለካከት፣ በብሔራዊ መረጣ ወይም በማኅበራዊ ማንነት ላይ ተመሥርቶ የሚደረግ ማንኛውም ልዩነት፣ ማግለል ወይም ማቅረብ (አንቀጽ 1(ሀ))፤ ወይም ያሉ ከሆነ ከአሠሪዎችና ከሠራተኞች ማኅበራት ጋር በመመካከር በሚመለከተው አባል ሊወሰን እንደሚችለው በሥራ ስምሪት ወይም በሙያ አያያዝ የዕድል እኩልነትን የመጉዳት ወይም ዋጋ የማሳጣት ዓላማ ወይም ውጤት ያለው እንዲህ ያለ ሌላ ልዩነት፣ ማግለል ወይም ማቅረብ (አንቀጽ 1(ለ))፡፡
    ይሁንና አንድ የተለየ የሥራ መደብ በሚጠይቃቸው ዋነኛ መስፈርቶች ላይ ተመሥርቶ የሚደረግ ማንኛውም ልዩነት፣ ማግለል ወይም ማቅረብ፣ መድልዎ እንደ ሆነ አይታሰብም (አንቀጽ 2)፡፡

    የተመድ የአካል ጉዳተኞች መብቶች ድንጋጌ በአካል ጉዳት ላይ ተመሥርቶ የሚፈጸም መድልዎን እንደሚከተለው ይገልጸዋል «በፖለቲካዊ፣ በኤኮኖሚያዊ፣ በማኅበራዊ፣ በባህላዊ፣ በሲቪል ወይም በማንኛውም ሌላ መስክ የሁሉንም ሰብአዊ መብቶችና መሠረታዊ ነፃነቶች እውቅና፣ ተጠቃሚነትና በሥራ ላይ መዋል የመጉዳት ወይም ዋጋ የማሳጣት ዓላማ ወይም ውጤት ያለው ማንኛውም ልዩነት፣ ማግለል ወይም ገደብ ማለት ነው፡፡ ይህም የተመጣጣኝ ማመቻቸት መንፈግን ጨምሮ ሁሉንም የመድልዎ ዓይነቶች ያካትታል፡» (አንቀጽ 2

    በሥራ ስምሪት የዕድልና የአያያዝ እኩልነት፡- ሁለት የእኩልነት አሠራሮች በሥራ ስምሪት ውስጥ አስፈላጊ ናቸው፤ እነዚህም የዕድል እኩልነትና የአያያዝ እልኩነት
    ናቸው፡፡ እኩል ዕድል ማለት አካል ጉዳተኞችን ጨምሮ ለአንድ የሥራ መደብ ለማመልከት፣ ለመቀጠር፣ ትምህርታዊና የሥልጠና ኮርሶችን ለመካፈል፣ አንዳንድ ብቁነቶች ላይ ለመድረስ ባለ መብት መሆን፣ እንደ ሠራተኛ ለመታየት፣ ወይም በሁሉም ሙያዎችና ቦታዎች ለእድገት ለመታሰብ እኩል አጋጣሚ ማግኘት ማለት ነው፡፡ በግለሰብና በቡድን መካከል ያሉት ልዩነቶች የታወቁ ሲሆን ማኅበራዊ ተሳትፎን ሊከለክሉ የሚችሉ አካል ጉዳተኞችን የሚያጋጥሙአቸው ውጫዊ መሰናክሎችም ግምት ውስጥ ገብተዋል፡፡ እኩል አያያዝ በክፍያ፣ በሥራ ሁኔታዎች፣ በሥራ ስምሪት ዋስትና እና በሌሎችም ባለመብት መሆንን ያመለክታል፡፡ የእኩልነት እድገት ኃይለኛ የሆኑ ቀጣይ ጥረቶችና የተጠባጭ እርምጃዎች ትግበራዎችን የሚጠይቅ ሲሆን ከመድልዎ ክልከላ ወይም መጥፋት ያለፈ እርምጃ ነው፡፡ በሥራ ስምሪትና በሙያ የሚፈጸም መድልዎን በሚመለከት በ1958 የወጣው የዓሥድ ድንጋጌ ቁ. 111 እና በሥራ ስምሪትና በሙያ የሚፈጸም መድልዎን በሚመለከት በዚሁ ዓመት የወጣው መሪ ሃሳብ 111 ዓለም አቀፍ መስፈርቶችን አስቀምጠዋል፡፡

    ተመጣጣኝ ማመቻቸት፡- አንዳንድ ጊዜ አካል ጉዳት በተለመደው ወይም መደበኛ በሆነው መንገድ ሥራን ለማከናወን የግለሰብን ችሎታ ይነካል፡፡ ተመጣጣኝ ወይም ውጤታማ ማመቻቸትን የማድረግ ግዴታ፣ ወይም ማመቻቸትን የማግኘት መብት፣ በዘመናዊው የአካል ጉዳት መድልዎ አልባ ሕግ ውስጥ አዘውትሮ የሚገኝ ነው፡፡ የአካል ጉዳት መድልዎ አልባ ሕግ አሠሪዎችና ሌሎች የአንድን ግለሰብ አካል ጉዳት ግምት ውስጥ እንዲያስገቡና የአንድ አካል ጉዳተኛ ሠራተኛ ወይም የሥራ አመልካች ፍላጎቶች ለማስተናገድ፣ እንዲሁም በተፈጥሮአዊውና ማኅበራዊ አካባቢ የተጋረጡትን መሰናክሎች ለማስወገድ ጥረቶች እንዲያደርጉ በይበልጥ ይጠይቃል፡፡ ይህ ግዴታ ተመጣጣኝ ማመቻቸት የማድረግ መለኪያ በመባል ይታወቃል፡፡ በሥራ ገበያው መሰናክሎች ለሚያጋጥሙአቸው ሠራተኞች ወይም የሥራ አመልካቾች ተመጣጣኝ ማመቻቸት ለማቅረብ አለመቻል መጥፎ የሥራ ስምሪት አሠራር ብቻ ሳይሆን ተቀባይነት እንደሌለው የሥራ ስምሪት መድልዎ ዓይነት በበለጠ እየታየ ነው፡፡  የተሳሳተ አተረጓጐም እንዲወገድና አሠሪዎች ምን ማድረግ እንዳለባቸው እንዲገነዘቡ ሕጉ በተመጣጣኝ ማመቻቸት ምን ማመልከት እንደ ተፈለገ በግልጽ ማብራራት ይኖርበታል፡፡ በተመድ የአካል ጉዳተኞች መብቶች ድንጋጌ አንቀጽ 2 ተመጣጣኝ ማመቻቸት «ያልተመጣጠነ ወይም ያልተገባ ሸክም መጫን ሳይሆን በተለየ ሁኔታ አስፈላጊ በሚሆንበት ቦታ የአካል ጉዳተኞችን ከሌሎች ጋር በእኩል ደረጃ በሰብአዊ መብቶችና መሠረታዊ ነፃነቶች ተጠቃሚነትና በሥራ ላይ መዋል ለማረጋገጥ አስፈላጊና ተገቢ የሆነ ማሻሻያ ወይም ማስተካከያዎች» እንደ ሆነ ተብራርቶአል፡፡ የተመጣጣኝ ማመቻቸት አሰጣጥ በዓይነቱ ጊዜያዊ መሆን የማይፈልግ የተለያየ እርምጃ ነው – በእርግጥ ለአንድ ግለሰብ በሥራ ስምሪት ቆይታው ወይም ቆይታዋ ሊሰጥ ይችላል፡፡ ተመጣጣኝ ማመቻቸት ለተወሰኑ ወገኖች ተስማሚ አያያዝ ከታቀደው የአዎንታዊ ተግባር እርምጃ ተለይቶ መታየት ይኖርበታል፡፡ ተመጣጣኝ ማመቻቸት የማቅረብ ግዴታ በጠቅላላ ተደራሽነት እንዲሁም በመያዊ ጤንነትና ደህንነት መስፈርቶች ከመስማማት ግዴታ ጋር መቀላቀል አይኖርበትም፡፡

    ያልተመጣጠነ ሸክም፡-  የአንድ አካል ጉዳተኛ ፍላጎቶችን ላለማመቻቸት የሚቀርብ «መከላከያ» ወይም ማረጋገጫ በጥንቃቄ መረቀቅ አለበት፡፡ አለዚያ ይሉኝታ ቢስ አሠሪዎች ማንኛውንም ግዴታ ለማስወገድ ይህን እንደ ፍንጭ ሊጠቀሙበት ይችላሉ፤ በርካታ ክሶችንም ሊያስከትል ይችላል፡፡ የሥራ ሰንጠረዥ እንዳይመች የሚደረግበት ሁኔታ በግልጽ ያልተመጣጠነ ሸክም ወደ መሆን አይደርስም፡፡ በአሠራር ሁኔታ ያልተመጣጠነ ሸክምን ምን ይፈጥረዋል የሚለው ጥያቄ በሚመለከተው ጉዳይ ጭብጥ ላይ የሚመረኮዝ ሲሆን በአንድ ማመቻቸት የገንዘብ ወጪዎች ወይም በገንዘብ ማካካሻ ዘዴዎች ላይ ብቻ የሚመረኮዝ አይደለም፡፡ ይልቁን ገንዘብ ነክ እንደምታዎቹን፣ አጠቃላይ የሥራ ሂደት ውጤቶቹን፣ አስቀድመው በተቀጠሩት አካል ጉዳተኛ ሠራተኞቹ ብዛትና በታሰበው የሥራ ስምሪት ውል ርዝመት በመሳሰሉት ጭብጦች ላይ ይመረኮዛል፡፡

    የአዎንታዊ ተግባር እርምጃ፡- አንዳንዴ ገንቢ እርምጃ የሚባለው ለተጎጂና ውክልና ለሌላቸው ወገኖች አባላት አማራጭ የአያያዝ መልክ በመስጠት የእኩል ዕድል መርሆን ለማሳደግ ይሻል፡፡ ገንቢ እርምጃ ለአጋጠመ መዋቅራዊ ወይም ተቅዋማዊ መድልዎ እንደ መልስ፣ እንዲሁም ለእኩል አያያዝ መርሆ እንደ ተረጋገጠ ልዩ ነገር በባህላዊው መንገድ ይታሰባል፡፡ በሌላ አነጋገር አዎንታዊ እርምጃ መድልዎ አይደለም፡፡ የአዎንታዊ ተግባር እርምጃዎች የዕድል እኩልነትን ለማሳደግ የሚሹ ሲሆን የተወሰኑ ወገኖች የሚያጋጥሙአቸውን መዋቅራዊ በደሎች ለማስወገድ የታቀዱ ናቸው፡፡ እንዲህ ያሉት እርምጃዎች የእያንዳንዱን ግለሰብ ፍላጎቶች ለማስተናገድ የታሰቡ ባለመሆናቸው በዚህ ከተመጣጣኝ ማመቻቸት የተለዩ ናቸው፡፡ የአዎንታዊ ተግባር እርምጃዎች በባህርያቸው ጊዜያዊ ሲሆኑ ማካካሻ እስከሚደረግበት ጊዜ ድረስ እንዲቆዩ፣ ወይም በመዋቅራዊ መልኩ ከተበደለው ባለ ሥራ መደብ መልስ ለማግኘት የታቀደ ነው፡፡