የሥልጠና ዝርዝር

6.2 መደበኛ ገለጻ - የምክክሩ ሂደት

  • የገለጻ ማሳያ 110ን በመጠቀም የዓይነተኛ ማርቀቅን/ምክክርን ደረጃዎች ይዘርዝሩ፡፡

    • ደረጃ አንድ፡- ሂደቱ ተለይቶ በመታወቅ ላይ ባለው ሕግ ወይም ፖሊሲ አስፈላጊነት ይጀምራል፡፡ ይህ ፍላጎት ተለይቶ የሚታወቀው በፖሊሲ አውጪዎች እና በሕግ አውጪዎች ወይም ከታች ባለው ኅብረተሰብ ሊሆን ይችላል፡፡ ይህ የምክክር ሂደቱ ጅምር ነው፡፡ ቁርጠኛ ፍላጎት ያላቸው ግለሰቦች ወይም ቡድኖች ለተወሰነ ሕግ ወይም ፖሊሲ የሚኖረውን ፍላጎት የመለየቱን ሃሳብ ሊያመነጩ የሚችሉ ሲሆን በዚህ የሂደቱ ደረጃ ላይ ተጨማሪ ባለ ድርሻዎችና ድጋፎችን ለይቶ ማወቅ ደግሞ አስፈላጊ ነው፡፡
    • ደረጃ ሁለት፡- የተነሡትን ጉዳዮችና ፍላጎቶች በሃሳብ መልክ ለመግለጽና ቅርጽ ለማስያዝ ይህ የሂደቱ ክፍል ነው፡፡ ከጅምሩ ይልቁን ቀላልና ባለ ፈርጀ ወጥ መስሎ የሚታየው ጉዳይ ውስብስብና ፈርጀ ሦስት ሆኖ ሊገኝ ይችላል፡፡ ይህ እርምጃ አንዳንድ ተጨማሪ ጭብጥ ፍለጋዎችን ያካትታል፡፡ ለምሳሌ እጅግ ዝቅተኛ የአካል ጉዳተኞች የሥራ ስምሪት መጠኖችን ለማሳየት ስታቲስቲኮች ሊጠቀሱ ይችላሉ፡፡
      ያ ክስተት ላይ ላዩን ሲታይ ለመድልዎ አልባነት ሕግና ፖሊሲዎች ያለውን ፍላጎት ሲመለክት ስታቲስቲኮቹ በእውነት ከአድላዊ አሠራሮች ጋር ፈጽመው የማይገናኙ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ምናልባት አገሪቱ በአካል ጉዳት ዋስትና (ኢንሹራንስ) ፕሮግራምና ሥራ ለመፈለግ የጥቅም ማግኛ መዝገቦችን እንዲተዉ ምንም ማትጊያዎችን በማይሰጠው የወቅቱ ፕሮግራም እየተሳተፉ ያሉ በርካታ አካል ጉዳተኞች ይኖሩአታል፡፡ ሌላው ቁልፍ ጉዳይ ካለው የሥራዎች ፍላጎት ጋር ለመመጣጠን ያሉት የሥራ ምደባ ድርጅቶች ብዛት የማይበቃ መሆኑ ነው፡፡ ቀዳሚ የሆነውን ችግር ለማረጋገጥና ተገቢ ሕግና ፖሊሲዎች ዒላማ ለማድረግ ጭብጥ ፍለጋው ወሳኝ ነው፡፡
    • ደረጃ ሦስት፡- ይህ ደረጃ የጉዳዩንና መዳሰስ የሚያስፈልጋቸውን ልምዶች ይበልጥ አጠቃላይ ሥዕል ማቅረብ ከሚችሉት ወገኖች ጋር ምክክርን ለማጣራት በመቀጠል ጉዳዩን መልክ በማስያዝ ይጀምራል፡፡  በዚህ ደረጃ ላይ የተጀመረው በጣም ውሱን ጉዳይ በጣም የተጠቃለለ ሊሆን ወይም በጣም በአጠቃላይ ሁኔታ ተጀምሮ ሊሆን የሚችለው በተጠየቀውና በተሰጠው ግብአት ላይ ተመርኩዞ ይበልጥ ውሱን ሊሆን እንደሚችል መገንዘብ አስፈላጊ ነው፡፡
    • ደረጃ አራት፡- ጉዳዮች አንዴ መልክ ካገኙ በኋላ የንድፈ ሃሳብ ወይም ነጭ ወረቀት ሊዘጋጅና ከዚያም በጉዳዩ ዙሪያ ስምምነት ላይ ለመድረስና የተፈለገውን ሕግ ወይም ፖሊሲ ቅርጽ ለማስያዝ ለሕዝብ ሊተዋወቅ ይችላል፡፡ ይህን የአቋም ወረቀት የሚጽፈው ማን በመሆኑ ዙሪያ የሚሰጠው ውሳኔ ጉዳዩ በሚታይበት ሁኔታ ላይ የተመረኮዘ ይሆናል፡፡ ጉዳዩ መሠረት ላይ ያረፈ ከሆነ የፖሊሲ አውጪዎችን ትኩረት ለመሳብ እንደ መሣሪያ ሊያገለግል ይችላል፡፡ ጉዳዩ በፖሊሲ አውጪዎች ተለይቶ ከታወቀ በጉዳዩ ዙሪያ የአቋም ወረቀት በማዘጋጀት እንዲረዱአቸው በኮንትራት ወደ ተዋዋሉአቸው ወይም ወደ ሕጋዊ አጣሪ አካላት ፊታቸውን ሊመልሱ ይችላሉ፡፡
    • ደረጃ አምስት፡- ጽንሰ ሃሳባዊ ዕቅዱን ሁሉም ባለ ድርሻዎች እንዲያውቁት ከተደረገ በኋላ ጉዳዮቹ በትክክል እንደ ተወከሉ ለማረጋገጥ ወረቀቱን እንደ ገና መመርመር አስፈላጊ ነው፡፡ ይህ የወረቀት ሥራዎቹ ደራሲ(ዎች) አስተያየቶቻቸው በወረቀቱ የተገለጹትን ክፍሎች የሚወክሉ መርማሪዎችን እንዲለዩ ከጠየቀው አካል ጋር ጉዳዮቹን፣ ሊሆኑ የሚችሉ መፍትሔዎችና ሕዝባዊ የፖሊሲ ስትራቴጂዎችን የመዘርዘሩን ሥራ በትክክል እንደ ሠሩ የሚያረጋግጡበት አሠራር ነው፡፡
    • ደረጃ ስድስት፡- የሕግ ወይም የፖሊሲ ዕቅድን ማጥራት የብዙዎችን ፍላጎቶች ማስተካከል የሚጠይቅ ወሳኝ ደረጃ ነው፡፡ ይህ ደረጃ ለሚመለከታቸው ወገኖች የጋራ ጠቀሜታዎችን ለማስከበር እንደሚደረግ ሙከራ የድርድርን ጥበብ ያጠቃልላል፡፡
    • ደረጃ ሰባት፡- በሚመረጥ ሁኔታ የመጨረሻው ደረጃ የአንድ ሕግ ወይም ፖሊሲ የመጀመሪያ ረቂቅ ነው፡፡ አንድ ረቂቅ ከመስመር ሚኒስቴሩ ወጥቶ ወደ ፍትሕ ሚኒስቴር ወይም ወደ ተመሳሳዩ፣ ወደ ካቢኔና አግባብነት ወዳለው ፓርላሜንታዊ ኮሚቴ ለውይይት ከመላኩ በፊት የምክክሩ ሂደት የተለያዩ ደረጃዎችን ሊያጠቃልል ይችላል፡፡ ረቂቅ ሕጉ የዳበረበት ሁኔታ ሕጉን በቀረጸው አገርና ምናልባትም ጉዳዩ እንደ ገና በሚታይበት ሁኔታ ላይ የተመረኮዘ ይሆናል፡፡

    በአካል ጉዳት ነክ ሕጎችና ፖሊሲዎች ዙሪያ የሚደረግ ምክክር አካል ጉዳተኞችንና ተወካዮቻቸውን እንዲሁም አካል ጉዳት ነክ አገልግሎት ሰጪዎችን እንደሚያካትት ለተሳታፊዎች ያስረዱ፡፡ ይህ ምክክር በሕጉ ዙሪያ ምክር ለመስጠት ልዩ ዓላማ በተቋቋሙ ገብረ ኃይሎች አማካይነት፣ ወይም የመንግሥት ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶችን በሚወክሉ ነባር ብሔራዊ ኮሚቴዎች ወይም ምክር ቤቶች እንዲሁም በአካል ጉዳተኞች ማኅበራትና ለእነርሱ በቆሙ ድርጅቶች አማካይነት ይከናወናል፡፡ በአንዳንድ ሁኔታዎች ምክክሩ በመንግሥት በሚጠራ ስብሰባ ወይም ስብሰባዎች አማካይነት በልዩ (አድ ሆክ) ሁኔታ ይካሄዳል፡፡

    ከላይ እንደ ተጠቀሰው አቀራረቦቹን ለመግለጽ በዐውደ ንባቡ ገጽ 63 የተዘረዘሩትን ከአውስትራልያ፣ ካምቦድያ፣ ቻይና፣ ኬንያ፣ ሞሪሽስ፣ ታንዛኒያ እና ታላቋ ብሪታኒያ የተገኙትን ምሳሌዎች ለማቅረብ የገለጻ ማሳያ 111ን ይጠቀሙ፡፡

    «በአውስትራልያ ብሔራዊ የአካል ጉዳት አማካሪ ምክር ቤት በቤተሰብና ማኅበረሰብ አገልግሎቶች ሚኒስቴር አማካይነት የጋራ ምጣኔ ሀብት መንግሥቱን ያማክራል፡፡ በ1996 የተመሠረተው ይህ ምክር ቤት አባላቱ በአካል ጉዳት ጉዳዮች ባላቸው ሙያና ችሎታ ላይ ተመሥርቶ ይመረጣሉ፡፡ ምክር ቤቱ ከተጠቃሚ ማኅበራት፣ ከቤተሰቦች፣ ከተንከባካቢዎችና ከአገልግሎት ሰጪዎች ጋር በዋነኛ የመንግሥት ተነሣሽነቶች ዙሪያ ምክክር በማመቻቸት ከፍተኛ ሚና ይጫወታል፡፡ እንዲሁም በመንግሥትና በግዛት ደረጃ ከሚንቀሳቀሱ ተመሳሳይ የአካል ጉዳት አማካሪ አካላት ጋር ግንኙነቶችን ያደርጋል፡፡»
    «በካምቦዲያ መንግሥትን በአካል ጉዳት ስልትና ሕግ አወጣጥ ዙሪያ ለማማከር፣ እንዲሁም ከአካል ጉዳት ጋር ተያያዥ በሆኑ ፕሮግራሞችና አገልግሎቶች እንደ አስተባባሪ ሆኖ ለመሥራት የአካል ጉዳት ተግባር ምክር ቤት በ1999 ተቋቋመ፡፡ የምክር ቤቱ አስተዳደር ቦርድ የመንግሥት፣ የአካል ጉዳተኞችና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ተወካዮችን ያካትታል፡፡ የአካል ጉዳት ተግባር ምክር ቤቱ ለተለዩ ዓላማዎች በተቋቋሙ የሥራ ቡድኖች በኩል ማኅበራዊ አጋሮችን ያሳትፋል፡፡»
    «በቻይና አካል ጉዳተኞችን የሚመለከቱ ሕጎችና ፖሊሲዎች በሚቀረፁበት ጊዜ መንግሥቱ የቻይና አካል ጉዳተኞች ፌዴሬሽንን፣ የመላው ቻይና የሠራተኞች ማኅበራት ፌዴሬሽንን እና የቻይና ኢንተርፕራይዝ ፌዴሬሽንን ያማክራል፡፡ በተጨማሪም ብሔራዊ ፖሊሲዎች በሚተገበሩበት ጊዜ ከአካል ጉዳተኞች ፌዴሬሽን፣ የሠራተኞችና የኢንተርፕራይዝ ማኅበራት ጋር ተደጋጋሚ ግንኙነት ይደረጋል፡፡»
    «በኬንያ ከአካል ጉዳተኞች ጋር የሚገናኙ ሕጎችን ለመመርመር በ1992 የአካል ጉዳተኞች ግብረ ኃይል ተቋቁሞአል፡፡ ቁልፍ ከሆኑት መሪ ሃሳቦች አንዱ የታቀደው የአካል ጉዳተኞች መጽደቅ ነበር፡፡ ይህን ስም የያዘው ሕግ ከአካል ጉዳተኞች ማኅበራትና ከአገልግሎት ሰጪዎች ጋር በተደረገ ተጨማሪ ሰፊ ምክክር በ2003 ጸድቆአል፡»
    «በሞሪሽየስ በ1996 በሕግ የተቋቋመው የአካል ጉዳተኞች ሥልጠናና የሥራ ስምሪት ቦርድ በብሔራዊ ፖሊሲ መተግበር ዙሪያ በመንግሥት ምክር ይጠየቃል፡፡ ይህ ቦርድ የአካል ጉዳተኞችና የሠራተኞች ተወካዮችን የያዘ ነው፡፡.»
    «በታንዛኒያ በአሠሪዎችና በሠራተኞች ማኅበራት አማካይነት በአካል ጉዳት ሕግ አጠቃቀም ረገድ ትብብር እንዲያደርጉ በሙያዊ ትምህርትና ሥልጠና ባለሥልጣንና በብሔራዊ አማካሪ ምክር ቤት በኩል ጥሪ ይደረግላቸዋል፡፡»
    «በታላቋ ብሪታኒያ የአካል ጉዳተኞችን ሕይወት የሚነኩ ችግሮችን መጠን ለመመርመር፣ አጠቃላይና የተጠናከሩ የሲቪል መብቶችን ለማሳደግ ምን ተጨማሪ እርምጃ መወሰድ እንዳለበት መንግሥትን ለማማከር የአካል ጉዳት መብቶች ግብረ ኃይል በታኅሣሥ 1997 ተመሥርቶአል፡፡»

    በመጨረሻ ውጤታማ ለመሆንና የአገሪቱን ፍላጎቶች በተጨባጭ ለማንጸባረቅ በአካል ጉዳት ነክ ሕግና ፖሊሲ ዙሪያ የሚደረጉ ምክክሮች ማኅበራዊ አጋሮችን፣ ማለትም የአሠሪዎችና የሠራተኞች ማኅበራት ተወካዮችን እንዲሁም አካል ጉዳተኞችን ደግሞ ማካተት ይኖርባቸዋል፡፡

    የማኅበራዊ አጋሮች ምልከታዎችን ለመግለጽ የገለጻ ማሳያ 112ን ይጠቀሙ፡፡ በተለያዩ አገሮች ያለውን የሠራተኛ ሕግ አወጣጥና የማሻሻል ሂደት በመመርመር የመጀመርን አስፈላጊነት አጽንኦት ይስጡ፡፡ እንዲህ ያሉት ምክክሮች በአንዳንድ ሁኔታዎች በነባር የሦስትዮሽ ክፍል አካላት አማካይነት ሲደረጉ በሌሎች ሁኔታዎች ደግሞ በተለይ ለዓላማው በተቋቋሙ አካላት ወይም ይበልጥ መደበኛ ባልሆኑ ዝግጅቶች አማካይነት ይካሄዳሉ፡፡ የሠራተኛ ሚኒስቴር ከማኅበራዊ አጋሮች ጋር ግንኙነት የሚያደርግ ሲሆን የነጭ ወረቀት አወጣጡ ሌላው የምክክር መንገድ መሆን ይችላል፡፡ አንዳንዴ የምክክሩ ሂደት በሕግ ማርቀቁ እንዲረዱ በተቀጠሩ ብሔራዊ ወይም ዓለም አቀፍ አማካሪዎች ይሻሻላል፡፡       

    በዐወደ ንባቡ ገጽ 64-65 በልዩ (አድ ሆክ) የሦስትዮሽ ክፍል ግብረ ኃይሎችና በነባር የሦትዮሽ ክፍል አካላት አማካይነት የሚደረጉትን የምክክር ምሳሌዎች ይጥቀሱና ያሳዩ፡፡

    በሦስትዮሽ ልዩ ግብረ ኃይሎች በኩል የሚደረግ ምክክር ምሳሌዎች፡-

    «በኬንያ በዓለም ሥራ ድርጅት ድጋፍ ወደ ተሻሻሉና አዳዲስ ሕጎች የሚያመራ የሠራተኛ ሕግ ማሻሻያ በተቀናጀ ሂደት በመካሄድ ላይ ነው፡፡ አዲሶቹ ሕጎች ኬንያ ካጸደቀቻቸው የዓለም ሥራ ድርጅት መስፈርቶች ጋር በሚስማማ መልኩ የተጠናከረ ማኅበራዊ ውይይትን ያበረታታሉ፡፡ በግንቦት 2001 የተቋቋመው የሦስትዮሽ የሠራተኛ ሕግ ግብረ ኃይል አዲሶቹ የሠራተኛ ሕጎች ምን መያዝ እንደሚኖርባቸው አገር-አቀፍ ምክክሮችን አካሂዶአል፡፡ በእነዚህ ምክክሮች ንቁ ተሳትፎ ነበር፡፡ መገናኛ ብዙኀን ለሕዝብ አስተያየት ጥሪ ባደረጉበት በመጀመሪያው ዙር ወደ 40 የሚጠጉ ተቅዋሞች፣ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችና ግለሰቦች አስተያየቶቻቸውን አጋርተዋል፡፡ ግብረ ኃይሉ የመጨረሻውን ሪፖርትና ረቂቅ ሕጎችን በ2004 ፀደይ ለሠራተኛና የሰው ኃይል ልማት ሚኒስቴር አቅርቦአል፡፡»
    «በኢንዶኔዢያ የእስያው የገንዘብ ቀውስና ዲሞክራሲያዊ የፖለቲካ ለውጦችን በመደገፍ የአምባ ገነን አገዛዝ መውደቅ ላመጣው ለውጥ መልስ በመስጠት በ1999 በሰው ኃይል ሚኒስቴር በሕግ የተቋቋመው የተጨማሪ-ሦስትዮሽ ግብረ ኃይል ተሳታፊዎች የመንግሥት፣ የአሠሪዎችና የሠራተኞች ተወካዮችን፣ እንዲሁም ፍላጎቱ ያላቸውን የሲቪል ኅብረተሰብ ወገኖች አካትቶአል፡፡ በሰው ኃይል መምሪያ አማካይነት በተካሄዱ ዐውደ ጥናቶች በሰፊው በሚያመካከር ሂደት የተጨማሪ-ሦስትዮሽ አባላት የሠራተኛ ሕጎቹን የመረመሩ ከመሆኑ በላይ ዲሞክራሲያዊና ዘመናዊ ለሆነው የሥራ ገበያ መልስ በሚሰጥ መልኩ አሻሽለዋቸዋል፡፡»

    በነባር የሦስትዮሽ አካላት አማካይነት የሚደረግ ምክክር ምሳሌዎች፡-
    «በደቡብ አፍሪካ ብሔራዊ የኤኮኖሚ ልማትና የሠራተኛ ምክር ቤት በ1995 ተቋቁሞአል፡፡ ምክር ቤቱ ድኅረ-አፓርታይድ መንግሥቱ በዋነኛ ኤኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊና የልማት ፖሊሲዎች ዙሪያ ወካይ አጠቃላይ የጋራ ስምምነት ላይ ለመድረስ የመሻቱን ቁርጠኝነት ያንጸባርቃል፡፡ በደቡብ አፍሪካ ከልዩ ፍላጎቶች አኳያ ምክር ቤቱ የማኅበረሰብ ፍላጎቶችን በሚወክሉ ባህላዊ ማኅበራዊ አጋሮች የተዋቀረ ነው፡፡ ዓላማዎቹ ከሥራ ገበያ ፖሊሲ ጋር ተያያዞ የቀረበ የሠራተኛ ሕግ ሁሉ ለፓርላመንት ከመቅረቡ በፊት መመልከትን ያካትታሉ፡፡ በአካል ጉዳትና በሌሎች ጭብጦች ላይ ተመሥርቶ የሚፈጸም መድልዎን የሚከለክለውን የ1998ቱን የሥራ ስምሪት ትክክለኛነት ሕግ ጨምሮ ምክር ቤቱ ሰፊ ረድፍ ባለው ሕግ ስምምነት ላይ ደርሶአል፡፡
    በሃንጋሪ የ1992ቱ የሠራተኛ ሕግ ለብሔራዊ የጥቅም ማስታረቂያ ምክር ቤት እውቅና ሰጥቶአል፡፡ ምክር ቤቱ ማኅበራዊ አጋሮችና የሠራተኛ ሚኒስቴርን የሚያቅፍ ሲሆን በሠራተኛ ግንኙነቶችና ብሔራዊ ጠቀሜታ ባላቸው የሥራ ስምሪት ጉዳዮች ላይ፣ በተለይም በአሠሪና ሠራተኛ ሕግ ማሻሻያ ላይ ምክክር መደረጉን የማረጋገጥ ኃላፊነት አለበት፡፡ ማኅበራዊ አጋሮች መረጃ የማግኘት በሕግ የተሰጠ መብትም አላቸው፡፡

    መደበኛ ዝግጅት ቢመረጥም ሆነ ወይም መደበኛ ያልሆነ አቀራረብ ቢወሰድ የምክክሩ ሂደት ለአካል ጉዳት ሕግ ወይም ፖሊሲ ፍላጎቱ ያላቸው ወይም በእርሱ የሚነኩ የተለያዩ ወገኖችን አንድ ላይ ለማሰባሰብ ልዩ ዕድል እንደሚሰጥ በማጠቃለል
    ይደምድሙ፡፡ ይህን መሰሉ የምክክር ሂደት መንግሥትን፣ የአሠሪዎችን፣ የሠራተኞችንና የአካል ጉዳተኞችን ተወካዮች እንዲሁም ፍላጎቱ ያላቸውን ሌሎች ወገኖች በማሳተፍ የተለያዩት ፍላጎቶች በሕጉና በፖሊሲው በበቂ ሁኔታ መንጸባረቃቸውን ለማረጋገጥ ረጅም መንገድ ይሄዳሉ፡፡

    ደግሞም የሕጉን ጽሁፍ ለማጠናቀቅ በተቻለ መጠን ስፋት ካለው የባለ ድርሻ ተሳትፎ ጋር የሚካሄዱ ሴሚናሮች ጠቃሚነታቸውን እንዳስመሰከሩ ይጠቁሙ፡፡ የሕግና ፖሊሲ አውጪዎች ማኅበራዊ አጋሮችንና ሲቪሉን ኅብረተሰብ ለማማከር አስፈላጊ ጥረቶችን ማድረግ ይኖርባቸዋል፡፡